በኦሮሚያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ችግሮች ላይ ያተኮረና የወደፊት የመፍትሄ ቅጣጫዎችን  የመላከተ ከፍተኛ የግብርና ባለሙያዎች የተሳተፉበት ሙያዊ ምክክር አውደ ጥናት ተካሄደ፡፡

በኦሮሚያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት ዋና መ/ቤት የስብሰባ አዳራሽ በተካሄደው በዚህ ስብሰባ ላይ የኦሮሚያ ግብርናና የተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ ሀላፊ ክቡር አቶ ዳባ ደበሌን ጨምሮ ከኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩትና ከኦሮሚያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት የተወጣጡ ከፍተኛ የግብርና ተመራማሪዎች፤በግብርና ሙያ የማማከር ስራ ላይ የተሰማሩ ከፍተኛ ባለሙያዎች ከተለይዩ ዩንቨርሲቲዎችና ከዓለም አቀፍ የግብርና ተቋማት የተወከሉ ተመራማሪዎችና የምርምር ዳይሬክተሮች በተሳተፉበት በዚህ የአንድ ቀን አውደ ጥናት ላይ ከላይ በተጠቀሰው አብይና ወቅታዊ አጀንዳ ላይ ሰፋ ያለ ውይይት አካሂደዋል፡፡

በዚህ ውይይት ላይ በክልሉ የግብርና ትራንስፎርሜሽን ችግሮች ምንድናቸው? እንዴትስ ሊፈቱ ይችላሉ? ከዚህም በላይ በግብርናው ላይ ሊገኝ የሚገባወን ለውጥ ለማምጣት የወደፊት አቅጣጫ ምን መሆን አለበት? በሚለው ርዕሰ-ጉዳይ ላይ የጋራ መግባባት ላይ ለመድረስ ሰፋ ያለ ውይይት ተካሂዷል፡፡

ለዘህ ውይይት መነሻ ሀሳብ የሆኑትን ጥናታዊ ጽሁፎች ለተሳታፊዎቹ ያቀረቡት ዶ/ር ማንደፍሮ ንጉሴ የኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተርና ዶ/ር መሀመድ ሀሰና የተቀናጀ የዘር ዘርፍ ልማት ፕሮግራም ምክትል ዋና ዳይሬክተር ናቸው፡፡

ከፍተኛ አጽንኦት በተሰጠው በዚህ ስበሰባ ላይ ከ35 በላይ ተመራማሪዎችና ከፍተኛ የግብርና ባለሙያዎች የተገኙ ሲሆን መድረኩን እንኳን ደህና መጣችሁ በሚል የመክፈቻ ንግግር ያስጀመሩት ዶ/ር ፈቶ ኢስሞ የኦሮሚያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ናቸው፡፡

 በውይይቱ ማጠቃለያ ላይ የክልሉ ግብርና በጤናማ አካሄዱ ውጤታማ ሆኖ በትራንስፎርሜሽኑ ዘመን መጨረሻ የታለመለትን የምርትና ምርታማነት ደረጃ ለመድረስ ማነቆ የሆኑ ችግሮች ተለይተውና አፋጣኝ መፍትሄ አግኝተው ወደ ሙሉ ትግበራ በመግባት ለውጤታማነቱ ሁሉም ሃለፊነቱን እንዲወጣ ከስምምነት ላይ ተደርሷል፡፡

በመጨረሻም ክቡር አቶ ዳባ ደበሌ ባደረጉት የመዝጊያ ንግግር የክልሉን የግብርና ትራንስፎርሜሽን ውጤታማ ለማድረግ በተለይ እያንዳንዱ ባለሙያ የራሱ ጥብቅ ሃላፊነት ያለበት መሆኑን በመግለጽ ከዚህ ጋር ልዩ ትኩረት ሊሰጠው የሚገባው ግብርናውን ለማዘመን መንግስት በግብርናው ላይ በሰፊው ኢንቭሰት በማድረግ ግብርናውን ብቻ ሳይሆን ህብረተሰባችንንም ወደ ተሸለ ደረጃ ማሳደግ እንደሚቻል ገልጸዋል፡፡